Friday 6 March 2015

መፃጉዕ (የዐቢይ ጾም አራተኛ ሳምንት)

የዐቢይ ጾም ስብከት (ክፍል 4)

በአያሌው ዘኢየሱስ


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ሰው ሁሉ በሥጋም ሆነ በነፍስ ታሞ ነበር፡፡ እርሱ ወደዚህ ዓለም የመጣው የሰው ልጆች ሁሉ አባትና መድኀኒት ስለሆነና ከዚህ በሽታቸው ሊያድናቸው ነው፡፡ ይህ ስለሆነ ወደ እኛ ከመጣ በኋላ ስለ መጣበት ዓላማ እንዲህ በማለት ተናገረን፡-   «. . . ለድሆች ወንጌልን እሰብክ ዘንድ ቀብቶኛልና፤ ለታሰሩት መፈታትን፣ ለዕውሮችም ማየትን እሰብክ ዘንድ፤ የተጠቁትንም ነጻ አወጣ ዘንድ፤ የተወደደችውንም የጌታን ዓመት እሰብክ ዘንድ ልኮኛል. . .» ሉቃ 4፥17-19፡፡ ይህ በመሆኑም መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድረ እስራኤል ተዘዋውሮ በልዩ ልዩ ደዌ የተያዙ በሽተኞችን ሁሉ አድኗቸዋል፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ ይህን ሁኔታ የገለጸው እንዲህ በማለት ነው፡- «. . . የመንግሥትንም ወንጌል እየሰበከ በሕዝብም ያለውን ደዌና ሕማም ሁሉ እየፈወሰ በገሊላ ሁሉ ይዞር ነበር፡፡ ዝናውም ወደ ሶርያ ሁሉ ወጣ፤ በልዩ ልዩ ደዌና ሥቃይም ተይዘው የታመሙትን ሁሉ፤ አጋንንት ያደሩባቸውን፤ በጨረቃም የሚነሣባቸውን ሽባዎችንም ወደ እርሱ አመጡ፤ ፈወሳቸውም፡፡» ማቴ 4፥23-24፡፡