Tuesday 30 September 2014

አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል

አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል
 መስከረም 20 ቀን 2007 ዓ.ም. 

በእግዚአብሔርና በሰው ልጆች መካከል የነበረውን የጥል ግድግዳ ያፈርስ ዘንድ ከአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን በኋላ ከሦስቱ አካል አንዱ አካል አምላካችን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ፤ እንደ ሕፃናት ቀስ በቀስ አድጎ፤ ወንጌልን ለዓለም ሰብኮ፤ ለሰው ልጆች ቤዛ ይሆን ዘንድ፤ በሞቱ ሞትን ይሽር ዘንድ፤ በመስቀል ላይ ተሰቀለ፡፡ በትንሣኤውም ለሰው ልጆች ትንሣኤን አወጀ፡፡ በእግዚአብሔርና በሰው ልጆች መካከል የነበረውንም የጥል ግድግዳ አፈረሰ፡፡ የሰው ልጆች ያጣነውን የእግዚአብሔር ልጅነትንም አገኘን፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “ወወሀብኮሙ ትዕምርተ ለእለ ይፈርኁከ ከመ ያመስጡ እምገጸ ቅስት ወይድኅኑ ፍቁራኒከ” ከቀስት ፊት ያመልጡ ዘንድ ለሚፈሩህ ምልክትን ሰጠሃቸው መዝ.49፡4 እንዲል፡፡ “ጠላቶቻችንን በአንተ ድል አናደርጋቸዋለን” በማለት የመስቀልን ክብርና አሸናፊነት አብስሯል፡፡መዝ. 43፡5፡፡

Gishen Debre Kerbe Mariam


Monday 22 September 2014

የመስቀል በዓል አከባበር በዩኔስኮ ቅርስነት ተመዘገበ

የመስቀል በዓል አከባበር በዩኔስኮ ቅርስነት ተመዘገበ
 ኅዳር 26 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ
  • የመስቀል በዓል አከባበር ኢትዮጵያ በዩኔስኮ ካስመዘገበቻቸው 10 ቅርሶች መካከል የመጀመሪያው የማይዳሰስ ቅርስ በመባል መመዝገቡን አስመልክቶ የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጠ፡፡
 0202023 1
የኢትዮጵያ የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን የኢትዮጵያ የመሰቀል በዓል አከባበር በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፤ የሳይንስና የባሕል ድርጅት (ዩኔስኮ) በማይዳሰሱ ቅርሶች (Intangible) በቅርስነት መመዝገቡን አስመልከቶ ኅዳር 26 ቀን 2006 ዓ.ም. በባለሥልጣኑ አዳራሽ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጠ፡፡

አቶ ዮናስ ደስታ የፌደራል የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ዳይሬክተር በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ “የመስቀል በዓል አከባበር በዩኔስኮ የማይዳሰስ ቅርስ (Intangible) ሆኖ የተመዘገበው ዩኔስኮ የሚጠይቀውን ሒደት ጠብቆና የተለያዩ የግምገማ መሥፈርቶችን አልፎ አዘርባጃን ዋና ከተማ ባኩ ከኅዳር 23 – 28 ቀን 2006 ዓ.ም. እያደረገ ባለው ስምንተኛው የዩኔስኮ የማይዳሰሱ ቅርሶች ጉባኤ ላይ በትናንትናው ዕለት ተቀብሎ አጽድቆታል”  በማለት ገልጸዋል፡፡

አቶ ዮናስ የመስቀል በዓል አከባበርን በቅርስነት ለማስመዝገብ የተደረገውን ጥረት ሲገልጹ በቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን ባለሙያዎች አማካይነት ጥናቱ ተከናውኖ ሰነዱ ለዩኔስኮ ዓለም አቀፍ ኖሚኔሽን  በ2004 ዓ.ም. መቅረቡን አውስተዋል፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ እንዲመዘገቡ ለጉባኤው ከቀረቡት 31 የማይዳሰሱ ቅርሶች መካከል 23ቱ ሲመረጡ የመስቀል በዓል አከባበር ከተመረጡት ውስጥ አንዱ በመሆኑና እውቅና ማግኘቱን ተናግረዋል፡፡

0202023 2አቶ ዮናስ የመሰቀል በዓል አከባበር በዓለም አቀፍ ደረጃ የመመዝገቡ ፋይዳን ሲገልጹም ቅርሱን የተመለከቱ መረጃዎች በዩኔስኮ ድረ ገጽ ላይ የሚለቀቅ በመሆኑ ሀገረ አቀፍና ዓለም አቀፍ እውቅና እንዲያገኝ እንደሚረዳው፤ የቱሪስት መስህብ መሆኑ፤ ከቀድሞ በተሻለ እንክብካቤ የሚደረግለትና ለትውልድ እንዲተላለፍ እገዛ ማድረጉን፤ ዓለም አቀፍ አጥኒዎችና ተመራማሪዎችን መሳቡ ዋና ዋናዎቹ  ጥቅሞች መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡

የሰሜን ተራሮች፤ አክሱም ጸዮን ሐውልቶች፤ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት፤ የታችኛው ኦሞ ሸለቆ፤ ጢያ ትክል ደንጋዮች፤ የታችኛው አዋሽ ሸለቆ፤ ሐረር ጀጎል፤ የኮንሶ ባሕላዊ መልክአ ምድር እና  የፋሲል ግቢ ኢትዮያ ከዚህ ቀደም ያስመዘገበቻቸው የሚዳሰሱ (tangible) ቅርሶች መካከል ዘጠኙ ሲሆኑ ብቸኛው የመስቀል በዓል አከባበር ከማይዳሰሱ ቅርሶች መካከል ይመደባል፡፡
 
 

ምንጭ

Saturday 20 September 2014

ጼዴንያ ማርያም

ጼዴንያ ማርያም

 

St.Mary“ሰላም ለሥዕልኪ እንተ ሠዓላ በእዱ፡፡ ሉቃስ ጠቢብ እምወንጌላውያን አሐዱ፡፡ አመ ተቀብዑ ማርያም እምሐፈ ሥዕልኪ ቅብዐ ናርዱ፡፡ በሕማም እኩይ እለ ደወዩ ወውሕዱ፡፡ ፅዑራነ ዓለም ጥዕዩ ወጥቀ ፈድፈዱ፡፡” አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም ዐሥር በዚች ቀን ጼዴንያ በምትባል አገር ሥጋ የለበሰች ከምትመስል ሥዕል ከሠሌዳዋ ቅባት እየተንጠፈጠፈ አምላክን የወለደች የእመቤታችን የድንግል ማርያም ተአምር ተገለጠ፡፡

ይቺንም ሥዕል የሣላት ወንጌላዊ ሉቃስ ነው፡፡ ወደ ጼዴንያ አገርም የመጣችበት ምክንያት አንዲት ስሟ ማርታ የሚባል መበለት ሴት ነበረችና ቤቷንም ለእንግዳ ማደሪያ ያደረገች ናት አምላክን የወለደች እመቤታችን ድንግል ማርያምንም እጅግ ትወዳት ነበር፡፡ በሚቻላትም ሁሉ ታገለግላታለች፡፡

በአንዲት ቀንም ስሙ ቴዎድሮስ የሚባል መነኲሴ ከእርሷ ዘንድ እንግድነት አደረ በመልካም አቀባበልም ተቀበለችው በማግሥቱም ስትሸኘው አባት ሆይ የምትሔደው ወዴት ነው አለችው፡፡ እርሱም በከበሩ ቦታዎች ውስጥ ልሰግድ ወደ ኢየሩሳሌም እሔዳለሁ አላት እርሷም ከአኔ ገንዘብ ወስደህ የእመቤታችን ማርያምን ሥዕል ግዛልኝና በመመለሻህ ጊዜ አምጣልኝ አለችው፡፡ እርሱም በራሴ ገንዘብ ገዝቼ አመጣልሻለሁ አላት፡፡

ከዚህም በኋላ ኢየሩሳሌም በደረሰ ጊዜ ከቅዱሳት መካናት ተባረከና ሥዕሏን ሳይገዛ ወደ ጐዳናው ተመለሰ፡፡ ያን ጊዜም ሥዕል መግዛትን ለምን ረሳህ የሚል የሚያስደነግጥ ቃልን ሰማ ወደ ገበያም ተመልሶ ላሕይዋና መልኳ ያማረና የተወደደ የሆነ የእመቤታችን ማርያምን ሥዕል አግኝቶ ገዛት በሐርና በንጹሕ ልብስም ጠቀለላት፡፡

በጐዳናውም እየተጓዘ ሳለ ከማያስፈራ ዱር ውስጥ ወንበደዎች ተነሡበት ሊሸሽም ወደደ ከዚያቺም ሥዕል መንገድህን ሒድ የሚል ቃል ወጣ የተከተለውም ሳይኖር መንገዱን ተጓዘ፡፡ ሁለተኛም ነጥቆ ሊበላው አንበሳ ተነሣበት ያን ጊዜም ከዚያች ሥዕል የሚያሥፈራ ድምፅ ወጥቶ አንበሳውን አባረረው፡፡

አባ ቴዎድሮስም ይህን ሁሉ ድንቅ ተአምር በአየ ጊዜ ያቺን ሥዕል ወደ አገሩ ሊወስዳት ወደደ ግዛልኝ ላለችው መበለት ይሰጣት ዘንድ አልፈለገም፡፡ ከዚህም በኋላ በመርከብ ተሳፍሮ በሌላ አቅጣጫ ሲጓዝ ታላቅ ነፋስ ተነሣበት ወደ ማርታ አገር ወደ ጼዴንያም ወሰደው ከመርከብም ወርዶ ከብዙ እንግዶች ጋር ወደዚያች መበለት ቤት ሔደ ማንነቱንም አልገለጣላትም እርሷም አላወቀችውም፡፡

በማግሥቱም ተሰውሮ ወጥቶ ወደ አገሩ ሊሔድ በፈለገ ጊዜ የቅጽሩን ደጃፍ አጥቶ ሲያጥመሰምስ ዋለ በመሸ ጊዜም ወደ ማደሪያው ተመለሰ፡፡ ያቺም መበለት በአየችው ጊዜ ታደንቃለች እንዲህም ሁኖ እስከ ሦስት ቀን ኖረ በመሸ ጊዜ በሩን ያየዋል ነግቶ መሔድን ሲሻ የበሩ መንገድ ይሠወረዋል፡፡ ያቺም መበለት ያዝ አድርጋ አባቴ ሆይ አእምሮህ ተነክቷልን ስትቅበዘበዝ አይሀለሁና ምን ሁነህ ነው አለችው፡፡

ከዚህም በኋላ ከዚያች ሥዕል የሆነውን ሁሉ ነገራት ራሱንም ገለጠላት፡፡ ያቺንም ሥዕል ሰጣት ተቀብላም የተጠቀለለችበትን ልብስ ፈታች ወዝ ከሥዕሊቱ ሲንጠፈጠፍ አገኘች፡፡ ከደስታዋም ብዛት የተነሣ የዚያን መነኲሴ እጆቹንና እግሮቹን ሳመች፡፡

ከዚህም በኋላ ያቺን ሥዕል ወደ ጸሎት ቤቷ ወስዳ በታላቅ ክብር የምትቀመጥበትን አዘጋጅታ አኖረቻት ማንም እንዳይዳስሳትም የነሐስ መስኮትን ሠራችላት በቀንና በሌሊትም የሚበሩ መቅረዞችን በፊቷ ሰቀለች ከመቅረዞም ውጭ የሐር መጋረጃን ጋረደች፡፡ ከሥዕሊቱ በታችም ከሥዕሊቱ እየተንጠፈጠፈ የሚወርደው የወዝ ቅባት የሚጠራቀምበት ከዕብነ በረድ የተሠራ ወጭት አኖረች ያም መነኰስ እስከሚሞትበት ቀን ድረስ የእመቤታችንን ድንግል ማርያምን ሥዕል እያገለገለ ኖረ፡፡

የሀገሩም ሊቀ ጳጳሳት የዚያችን ሥዕል ዜና በሰማ ጊዜ ከኤጲስ ቆጶሳትና ከካህናት ከሕዝቡም ሁሉ ጋር መጣ፡፡ በሠሌዳዋም ውስጥ በአዩዋት ጊዜ ሥጋ የለበሰች ሁና አገኙዋት ከዚህ ከአምላካዊ ግብር የተነሣ አደነቁ ከዚያም ቅባት ቀድተው ለበረከት በተካፈሉ ጊዜ ወዲያውኑ በወጭቱ ውስጥ ይመላል፡፡

ወደ ሌላ ቦታም ሊወስዷት በፈለጉ ጊዜ ንውጽውጽታ ሁኖ ብዙዎች በድንጋጤ ወደቁ ሥዕሊቱም እስከ ዛሬ በዚያች አገር ትኖራለች፡፡ ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በእናቱ በእመቤታችን በድንግል ማርያም ጸሎት ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን፡፡
  • ምንጭ፡- መጽሐፈ ስንክሳር ከመስከረም እስከ የካቲት