Wednesday 4 April 2012

ሆሣዕና በዲ/ን ቀለመወርቅ ሚደቅሳ


Hosahna.JPG
በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት የዐቢይ ጾም ሳምንታት የየራሳቸውን ምክንያት መሠረት በማድረግ ልዩ ልዩ ስያሜዎችን ይዘው እናገኛቸዋለን፡፡ በዚህም መሠረት የሰሙነ ሕማማት ዋዜማው ሰንበት ሆሣዕና ተብሎ ይታወቃል፡፡ በዚህም አምላክ ወልደ አምላክ ሥግው ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ የጽድቅ የትሕትና እና የፍቅር ንጉሥ ሆኖ ወደ ኢየሩሳሌም የገባበት ነው፡፡ /ማቴ.21÷1፣ ማር.11÷1፣ ሉቃ.19÷23፣ ዮሐ.12÷12/


በዚህ ዕለት አይሁድ ጌታ ወደ ኢየሩሳሌም እንደሚመጣ በሰሙ ጊዜ የዘንባባ ዝንጣፊ ይዘው ሊቀበሉት ወጥተዋል፡፡ /ዮሐ.12÷12/ ዘንባባ የድል ማብሠሪያ ምልክት ነው፡፡ ጌታ የጨለማውን ኃይል በሞቱ ድል የሚነሣ ነው፡፡ የድል አድራጊነት ዘንባባ የተገባው ለዚህ ነው፡፡ የደስታችን ምንጩ ደስታን ለሚሰጥ ለእርሱ የደስታ መግለጫ ዘንባባ ቀረበለት፡፡ ሰላምን ደስታን ለዓለም ሁሉ የሚያድል ሰማያዊ ንጉሥ ክርስቶስ ነው፡፡ ከሞትና ከመበስበስ ጠብቆ ዘለዓለማዊውን ደስታ ያደለ ክርስቶስ፡፡

በዚህ የነበሩትም /መዝ.117÷25/ ያለውን የትንቢት ቃል እየዘመሩ ጮሁ፡፡ ይህም ይመጣል የተባለውን መሲህ እንዴት በጉጉት እየጠበቁት እንደነበር የሚያስረግጥ ነው፡፡ ክብር እንደሚሻ ደሀና የተዋረደ ሆኖ ቢመጣም እንደ ንጉሥ እና የእስራኤል አዳኝ ተቀበሉት፡፡ እንደ የጽድቅ ንጉሥ ተቀበሉት፡፡ ሆሣዕና አያሉም ጮኹ፡፡ ክርስቶስ መድኃኒት የሆነ ንጉሥ ነው፡፡ የጎሰቆለውን የሰውን ሰውነት የሚያድን የአርያም መድኃኒት፡፡ በዚህም በመዝሙራቸው ከዳዊት ጋር ተባበሩ፡፡ /መዝ.23÷7/

“በጌታ ስም የሚመጣ የእስራኤል ንጉሥ የተባረከ ነው” ጌታ ነውና በራሱ ስም መጣ፡፡ /ዮሐ.1÷1/ እስራኤል የንጉሣቸውን መምጣት በተንሸዋረረ መንገድ ይጠብቁት ስለነበር መምህራነ አይሁድ አልወደዱትም፡፡

ክርስቶስ የእስራኤል ንጉሥ መሆን ምን የሚረባው ሆኖ ነው? ክርስቶስ የእስራኤል ንጉሥ በመሆን ግብር የሚሰበስብ ወታደር በማደራጀት ጠላቶቹ ላይ ጦርነት የሚያውጅ አይደለም፡፡ ቢያምኑበት ቢታዘዙት የልቦናቸው ንጉሥ ሊሆን መጥቷል፡፡ እምነት ተስፋ ፍቅርን ገንዘብ ቢያደርጉ የሰማያዊ መንግሥቱ ዜጎች ሊያደርጋቸው የጽድቅ ንጉሥ ሆኖ መጣ፡፡ ሐሰትን በመናገር ሳይሆን ጽድቅን /እውነትን/ በመስበክ የነገሠ ንጉሥ ነው፡፡ ወልደ እግዚአብሔር ዓለም በእርሱ ቃልነት የተፈጠረ የዓለም ሁሉ ንጉሥ በፈቃዱ የእስራኤል ንጉሥ ተባለ፡፡ በምድር የእስራአል ንጉሥ የተባለ ክርስቶስ በሰማያትም የመላአክት ንጉሥ ነው፡፡

“አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ÷ አትፍሪ፤ እነሆ÷ ንጉሥሽ በአህያ ውርንጫ ላይ ተቀምጦ ይመጣል” /ዮሐ.12÷15/ ጌታ ብዙ ጊዜ ከቦታ ቦታ ሲዘዋወር የተጓዘው በእግሩ ነው፡፡ አሁን ግን አስደናቂ በሆነ ሁኔታ በአህያ ውርንጫ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ገባ፡፡ ትሑት ንጉሥ ኢየሱሱ ክርስቶስ፡፡ ንጉሥ ተብሎ ወደሚከብርበት ቦታ ሲያመራ አምሮ÷ ተውቦ፤ በአማረ ልብስ÷ በአማረ መጓጓዣ የማይሄድ ትሑት ንጉሥ ክርስቶስ፤ በአህያ መቀመጡ ብቻ ሳይሆን አህያይቱ እንደ ሰሎሞን አህያ በተዋቡ ቁሳቁስ ያጌጠች አልነበረችም፡፡ /መኃ.መኃ.3÷9/ የክርስቶስ ክብር በቁሳዊ ነገር የሚገለጥ አይደለም፡፡ መንግሥቱ ሰማያዊ እንጂ ምድራዊ አይደለምና በምድራዊያን ነገሥታት የንግሥና ወግ ልብስና ጌጥ አልመጣም፡፡ እጅግ ትሑት ንጉሥ አምላካችን ክርስቶስ ነው፡፡

ነቢዩ የጽዮን ልጅ እንድትነሣ ልቦናዋን በድል አድራጊነት ደስታ የሚሞላትን ንጉሥ እንድትቀበል ያዛታል ስለዚህ ፈፅማ እንድትደሰት ጠየቃት፡፡ ፍርሃቷንና ሀዘኗን የሚያጠፋ ንጉሥ መጥቷልና፡፡ የነቢዩ ዘካርያስ ትንቢት በዚህ ፍፃሜውን አገኘ፡፡ /ዘካ.9÷9/ ክርስቶስ ከሮማውያን ወይም አይሁዳውያን ጠላት የሆኑትን ሊበቀል የመጣ አይደለም፡፡ ሰማያዊ ሰላምና ክብር ሊያጎናፅፋቸው እንጂ፡፡ ይህንን ቅዱስ ሉቃስ “በሰማይ ሰላም በአርያምም ክብር” በማለት የገለጠው ነው፡፡ /ሉቃ.19÷38/ ጠላቶቹን እስከ መስቀል ሞት የወደደ የፍቅር ንጉሥ በመግደል ሳይሆን በመሞት በልቦናችን የነገሠ የፍቅር ንጉሥ ክርስቶስ ነው፡፡

“አትፈሪ” የሚመጣው የሚያከብራት ነውና ፍርሃትን እንድታስወግድ ተበሰረች፡፡ እርሱ መከራዋን ለመቀበል ደሙን በማፍሰስ ኃጢአትን ሊደመስስ ሕይወትን ሊሰጣት መጥቷልና አትፍሪ ተባለች ቤተ አይሁድ፡፡ ውርንጫይቱ ቀድሞ ምንም ጭነት የማያውቃቸው ሕግን ያልተቀበሉ በሕግ ያልኖሩ አሕዛብ ምሳሌ፤ አህያይቱ ጭነት የለመደች ሕግና ሥርዓት ተሰርቶላቸው የነበሩ የእስራአል ምሳሌ ናቸው፡፡ /ቅዱስ አውግስጢኖስ/“ የጽዮን ልጅ ሆይ አትፍሪ” አለ፡፡ ቀድመው አይሁድ ላይ ነግሠው የነበሩ ጨካኞች እና ኢፍትሐዊያን ስለ ነበሩ፡፡ ለጠላቶቻቸው አሳልፈው የሰጧቸው ነገሥታት ስለነበሩ፡፡ ክርስቶስ ግን የፍትሕ እና የርሕራሔ ንጉሥ ሆኖ መጥቷል፡፡ /ቅድስ ዮሐንስ አፈወርቅ/
“ደቀ መዛሙርቱ ግን ይህ ሁሉ ሲሆን አላስተዋሉም ነበር እስከ ጌታ ትንሣኤም በዚሁ ያለመረዳት ጉዞ ገፈተውበታል” /ዮሐ.12÷16/ ሐዋርያት በወቅቱ የተፈፀሙትን ተግባራት እውነተኛ ምሥጢራቸውን ለማስተዋል አለመብቃታቸውን ወንጌላዊ ነገረን፡፡ በወቅቱ ሐዋርያት በዙሪያቸው የሚፈጸሙ ተግባራት እውነተኛ ምንነታቸው እንደማይረዱ ሕፃናት ነበሩ፡፡ በኋላ በጌታ ስቅለት÷ ትንሣኤና እርገት በእውቀት እና በመንፈስ ቅዱስ በጎለመሱ ጊዜ በዕለተ ሆሣዕና የሆነውን ሁሉ ተረዱ፡፡ “ነገር ግን ጌታችን ከከበረ በኋላ በዚያን ጊዜ ይህ ሁሉ ስለ እርሱ እንደተፃፈ ይኸንም እንዳደረጉለት ትዝ አላቸው” ዮሐ.12÷17/ የእግዚአብሔርን ምሥጢር ለመረዳት ትንሣኤ ልቡና ያስፈልጋል፡፡

በዓለ ሆሣዕና ክርስቶስ የጽድቅ የትሕትና እና የድኅነት ንጉሥ እንደሆነ በአደባባይ የተገለጠበት ነው፡፡ ሕዝብና አሕዛብን አንድ ለማድረግ እንደመጣ በምሥጢር የገለጠበት ዕለት ነው፡፡

ሐዋርያት በጌታ ትንሣኤና እርገት ምሥጢር እንደተረዱ የፍቅር የትሕትና እና ድኅነት የሆነ የክርስቶስን ነገር በትንሣኤ ልቡና ተረድተን የሰማያዊ መንግሥቱ ዜጎች ለመሆን ያብቃን አሜን፡፡ 

No comments:

Post a Comment