Sunday 8 April 2012

ሥርዐተ ሰሙነ ሕማማት


                                ሥርዐተ ሰሙነ ሕማማት

(ምንጭ ስምዐ ጽድቅ ልዩ እትም ዘሰሙነ ሕማማት መጋቢት 2002 :: 
ስንክሳር-  የዲያቆን መልአኩ እዘዘው ገጽ )

ሥርዐት ምንድን ነው?

ወንድሞች ሆይ፡ ከእኛ እንደተቀበለው ወግ ሳይሆን ያለ ሥርዓት ከሚሔድ 
ወንድም ትለዩ ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እናዛችኋለን። 
በእናንተ ዘንድ ያለሥርዐት አልሔድንምና። “ (2 ተሰ. 3 6)


           ሥርዐት የሥነ ፍጥረት ሕይወት ምሕዋር፣ መቆጣጠሪያ መሣሪያ ነው። 
የመዓልቱ በሌሊት፣ የሌሊቱ በመዓልቱ በመሠልጠን ሥርዓተ ዑደትን 
እንዳይጥስና የመዓልቱ በመዓልቱ የሌሊቱ በሌሊት እየተመላለሰ 
ዕለታዊ ግብሩን እንዲያከናውን ማንኛውንም ፍጡር ፈጣሪው በሥርዐት 
አሰማርቶታል። (መዝ. 10519-24)  

           
በተለይ መንፈሳዊያን ልዑካን መንፈሳዊውን ተልእኮ ያለ ሥርዓትና 

ያለ ሕግ ማካሔድ እንደማይችሉና እንደማይገባም ሐዋርያው አስተማረ። 
ያለ ሥርዐት ከሚካሔድ ወንድም ተለዩ” አለ። ስለሆነም በሰሙነ ሕማማት
 የሚከናወኑ ሃይማኖታዊ እሴቶች ከዚህ ኃይለ ትምህርት የተገኙ መሆናቸውን 
እያሰብን በሰሙነ ሕማማት የሚከናወኑ የሕማማት ሥርዐቶችን ቀጥለን 
እንመለከታለን።
ሰሙነ ሕማማት

           ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከዕለተ ትንሣኤ በፊት ያለውን ሳምንት 
ሰሙነ ሕማማት በማለት ታከብረዋለች። የዚህ ስያሜ መነሻም የጌታችን
 የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስመከራው፣ሕማሙና ሞቱ የሚዘከርበት
 ከአዳም እስከ ክርስቶስ የነበረው የዓመተ ፍዳ የዓመተኩነኔ ወቅትም 
የሚታሰብበት ስለሆነ ሰሙነ ሕማማት ተብሏል። የዚህ ጾም መነሻም 
በፍትሐነገሥት አንቀጽ 15 ላይ ተደንግጓል። ጥንታዊ ቀዳማዊ 
መሆኑም ይታወቃል።
በሕማማት የማይፈቀዱ
           በዚህ በሰሙነ ሕማማት ሳምንትም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን 
ለየት ያለ የአገልግሎትሥርዐት ሠርታለች ከጸሎተ ሐሙስ በቀር ቅዳሴ 
አይቀደስም። ይህ ብቻ አይደለም። የዘወትርየቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሎት 
የሆነው ሥርዐተ ጥምቀተ ክርስትና፣ ሥርዐተ ፍትሐት፣ሥርዐተ ማኅሌት፣
ሥርዐተ ተክሊልና ሌሎችም የተለመዱ አገልግሎቶች አይካሔዱም።
በመስቀል መባረክ፣ ኑዛዜ መስጠትና መቀበል፣ 
እግዚአብሔር ይፍታህ ማለትየለም።በአጠቃላይ ከዓመት እስከ 
ዓመት በቅድስት ቤተ ክርስቲያን አማካይነት ለምዕመናንይሰጡ 
የነበሩ መንፈሳዊ አገልግሎቶች አቁመው በሌላ ወቅታዊ ማለትም 
የጌታችንንሕማሙን መከራውን መከሰሱን መያዙን ልብሱን 
መገፈፉን (ስዕል 2 ተአስሮ ድኅሪትበጲላጦስ አደባባይ መቆሙን፤ 
መስቀል ላይ መዋሉን ሐሞት መጠጣቱን እና ሌሎችንም ለኅጢአተኛው 
የሰው ልጅ ሲባል የተከፈለውን ዕዳ በሚያስታውሱ አገልግሎቶችይተካሉ።
እነዚህንም ሥርዐታዊና ምስጢራዊ የሰሙነ ሕማማት አገልግሎቶች 
ከዕለተ ሆሳዕና እስከ ቀዳም ሥዑር ድረስ እንዴት እንደሚከናወኑ 
በኣጭር በአጭሩ እንመለከታለን።

ዕለተ ሆሣዕና

              ሆሣዕና በአርያም ማለት በአርያም/በሰማይያለ መድኃኒት ማለት ነው። ጌታችንበአህያ ውርንጫ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም የገባበት ዕለት ከዘጠኙ ዐበይት በዓላት አንዱስለሆነ የከበረ በዓሉ ምስጋና በዋዜማው ይጀመራል። ቅዳሜ ከሰዓት በኋላ ካህናቱ “በእምርትዕለት በዓልነ  በታወቀ የበዓላችን ቀን ከበሮ ምቱ” በማለት የዋዜማውን ምስጋና ቀለም እጅግሰፊ ስለሆነ በዚህ መዘርዘር አይቻልምና ከዋዜማው ፍጻሜ በኋላ ያለውን ሥርዐትእንመለከት።

               በሌሊት ሆሣዕና ማኅሌት ከመቆሙ በፊት በካህኑ ተባርኮ በሰሙነ ሕማማትሲነበብ ሲተረጉም የሚሰነብተው ግብረ ሕማማት የተባለው መጽሐፍ መነበብ ይጀምራል።ስቡሕ ወውዱስ ዘሣረረ ኩሎ ዓለመ፤ ዓለምን ሁሉ የፈጠረ እግዚአብሔር ፍጹም የተመሰገነነው። በሚለው የምስጋናዎች ሁሉ ርዕስ የዕለቱ የማኀሌቱ ምስጋና በካህናት በሊቃውንትይጀመራል። ከዐቢይ ጾም መግቢያ ጀምሮ ማዕቀብ ተጥሎባቸው በዝምታ የሰነበቱት ከበሮናጸናጽል የምሥጋናው ባለ ድርሻዎች ይሆናሉ በዚህ የተጀመረው ማኅሌት ሌሊቱን ሙሉአድሮ መዝሙር በሚባለው…... ምስጋና በኩል አድርጎ ሥርዐተ መወድስ ተደርጎ ሰላምበተባለ የምስጋና ማሳረጊያ ይጠናቀቃል።

ሥርዐተ ዑደት ዘሆሣዕና

                  ሥርዐተ ማኅሌቱ ተፈጽሞ ሥርዐተ ቅዳሴው ከመጀመሩ በፊት እስከ አሁንከነበረው ሥርዐት ለየት ያለ ሆኖ እንመለከታለን። ይኼውም ሊቃውንቱ የዕለቱን ድጓ እየቃኙእየመሩና እየተመሩ፣ ዲያቆኑ ከመዝሙረ ዳዊት የዕለቱን በዓል የተመለከተ ምስባክ በዜማእያሳመረ፣ ካህናቱ በዓሉን የተመለከተ ወንጌል በአራቱም መዓዘን እያነበቡ ቤተ መቅደሱንአንድ ጊዜ ይዞሩታል። ለምሳሌ ከምዕራብ ወደ ምሥራቅ ባለው በር ፊት ለፊት በመቆምመምህሩ “አርእዩነ ፍኖቶ ወንሑር ቤቶ፤ ወደቤቱ እንገባ ዘንድ መንገዱን አሳዩን፡፡የሚለውን ድጓ ይቃኛሉ ካህናቱ እየተከተሉ ያዜማሉ ዲያቆኑ “ዘመሩ ለእግዚአብሔርዘየሐድር ውስተ ጽዮን  በጽዮን የሚገለጥ እግዚአብሔርን አመስግኑ” እያለ ያዜማል፡፡ካህኑም (ማቴዎስ ወንጌል 21÷1-13) ያለውን ኀይለ ቃል ያነባል፡፡ በዚህ አይነት መልክበአራቱም መዓዘነ ቤተ ክረስቲያን ሥርዐተ ዑደቱ ይፈጸማል፡፡

              ይህን ሥርዐት ሊቃውንቱ ሲተረጉሙት አንደኛ ጌታችን በአህያ ውርንጫ ተጭኖበሕፃናት አንደበት እየተመሰገነ ኢየሩሳሌም የገባበትን የምሥጋና ጉዞ ለማመልከት ሲሆንሁለተኛ ሕገ ወንጌል በአራቱም መዓዘነ ዓለም ለሕዝብ ለአሕዛብ መዳረሱን ለማመልከትናሕዝብና አሕዛብ በሕገ ወንግል አንድ አካል ማሆናቸውን በገቢር ለማሳየት መሆኑንያስተምራሉ፡፡

ሥርዓተ ቅዳሴ ዘሆሣዕና

               
በዕለተ ሆሣዕና አሁንም የቅዳሴው አገባብ ሥርዓት ከሌሎች ዕለታት ለየት ያለመሆኑን እንመለከታለን ዲያቆናቱ ሕብስቱን በመሶበ ወርቅ ወይኑን በጽዋዕ ይዘው በምዕራብበር በኩል ይቆማሉ ሠራኢው ዲያቆን በዜማ አሰምቶ “አርኅው ኈኀተ መኳንንት አለቆችደጆችን /በሮችንክፈቱ” ይላል፡፡ ካህኑም በመንጦላዕት ውስጥ ሆኖ “መሉ ውእቱ ዝንቱንጉሠ ስብሐት ይህ የክብር ንጉሥ ማን ነው” ብሎ ይጠይቃል ዲያቆኑም “ይህ የክብር ንጉሥየኃያላን አምላክ እግዚአብሔር ነው” ብሎ ይመልሳል ዲያቆኑ ሦስት ጊዜ የከፈቱልኝጥያቄያዊ ዜማውን ካዜማ በኋላ ካህኑ “ይባዕ ንጉሠ ስብሐት፤ የክብር ንጉሥ ይግባብሎፈቅዶለት ይገባል፡፡
             ይህንንም አበው እንደሚከተለው ያመስጥሩታል:: አንደኛ ቅዱስ ገብርኤልናወላዲተ አምላክ በምሥጢረ ብስራት ጊዜ የተነጋገሩት እንደሆነና በመጨረሻም ይኩነኒ በከመትቤለኒ፣ እንደ ቃልህ ይደረግልኝ ብላ መቀበሏን ሲያሳይ ሁለተኛው ፈያታይ ዘየማንናመልአኩ ኪሩብ በማእከለ ገነት የተነጋገሩትን በድርጊት ለማሳየት መሆኑን ያስተምራሉ፡፡ዋናው ምሥጢር ግን ክርስቶስ ወደ ቤተ መቅደስ ሊገባ ሲል ብዙዎቹ እንዳይገባ ቢፈልጉምከፊሎቹ ግን እንዲገባ መፍቀዳቸውን ያሳያል፡፡

             እንደተለመደው ሥርዐተ ቅዳሴው ከተጠናቀቀ በኋላ እግዚአ ሕያዋን /የሕያዋንጌታየሰኘው ጸሎት በካህናት ተደርሶ ለምእመናን ሥርዐተ ፍትሐት ይደረግላቸዋል፡፡ከዚያ በኋላ ሥርዐተ ፍትሐት ስለማይደረግ፡፡ በሰሙነ ሕማማት የማይከናወኑ ምሥጢራትበዕለተ ሆሣዕና ይከናወናሉ፡፡

              ምእመናንም ተባርኮ የተሰጣቸውን የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ ወደየቤታቸውያመራሉ የዘንባባው ምሥጢር የተጀመረው በታላቁ አባት በአብርሃም ነው፡፡ ኩፋ.1321ይህን የአባታቸውን ሥርዐት አብነት አድርገው እስራኤል የኤርትራን ባሕር ሲሻገሩ፣ ዮዲትድል በአደረገች ወቅት ዘንባባ እየያዙ እግዚአብሔርን አመስግነውበታል። ጌታችን በዕለተሆሣዕና ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባም ሽመግሌዎችና ሕፃናት የዘንባባ ዝንጣፊ ይዘውእንደተቀበሉት እናነባለን፡፡ (ሉቃ.12 8)

             ኢትዮጵያውያን ምእመናንም ክርስቶስ የሰላም የነጻነት የድኅነት አምላክ መሆኑንለመመስከር ዘንባባውን ይዘው ወደቤታቸው ይሄዳሉ፤ እንደቀለበትያሠሩታል፤ያሠሩታልም። አሁን ደግሞ ወደ ሌሎች ዕለታት ሥርዐት አንሻገር፡፡

ዕለተ ሰኑይ/ሰኞ/ በነግህ

             ከሁሉም በፊት የሰዓቱ ተረኛ አገልጋይ ቃጭል እየመታ ሦስት ጊዜ ቤተክርስቲያኑን ይዞራል የሰባት ቀን ውዳሴ ማርያም፣ አንቀጸ ብርሃን፣ መዝሙረ ዳዊት በሙሉይጸለያል በዕለቱ ተረኛ መምህር /መሪጌታየዕለቱ ድጓ ይቃኛል:: ድጓው ከአራቱ ወንጌላትምንባብ ጋር እንዲስማማ ሆኖ ነው የሚቃኘው ድጓውን እየተቀባበሉ እያዜሙ ይሰግዳሉየድጓው መሪ መምህር ሰኞ በቀኝ ከሆነ ማክሰኞ በግራ በኩል ባለው መምህር ይመራልእንዲህ እየተዘዋወረ ይሰነብታል ድጓው ሦስት ጊዜ ተመላልሶ ከተዘለቀ በኋላ፡-


ለከ ኀይል ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለመ ዓለም

አማኑኤል አምላኪየ ለከ ኃይል ክብር ወስብሐት ወእዘዘ እስከ ለዓለመ ዓለም፡፡

 እግዚእየ ኢየስስ ክርስቶስ ለከ ኃይል ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለመ ዓለም::

ኀይልየ ወጸወንየ ውእቱ እግዚእየ እስመ ኮንከኒ ረዳእየ እብል በአኮቴት

እየተባለ በቀኝ በኩል ስድስት፣ በግራ በኩል ስድስት ጊዜ እየተዜመ ይሰገዳል፡፡ በድምሩ12 ጊዜ ማለት ነው በዚያው ልክ አቡነ ዘበሰማያት በዜማ /በንባብይደገማል፡፡ ከዚያበመቀጠል

ለአምላክ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለመ ዓለም
ለሥሉስ ይደሉ ክብር ወስብሐተ ወእዘዘ እስከ ለዓለመ ዓለም
ለእዘዙ ይደሉ ክብር ወስብሐተ ወእዘዝ እስከ ለዓለመ ዓለም፡፡
                        ለመንግሥቱ፣ ለሥልጣኑ፣ ለምኩናኑ፣ ለኢየሱስ፣ ለክርስቶስ፣ ለሕማማ፣/ለዓርብ ለመስቀሉይደሉ 

እያሉ በቀኝ በግራ እየተቀባበሉ ይሰግዳሉ በመቀጠል የነግሁ ምንባብ መነበብ ይጀምራልበመጨረሻ ተአምረ ማርያምና ተአምረ ኢየሱሰ ይነበባሉ ከዚያ ከዳዊት መዝሙር መስባክተሰብኮ የሰዓቱ ወንጌል ከተነበበ በኋላ ጸልዩ በእንተ ጽንዓ ዛቲ የተባለው ጸሎት በካህኑ ሲነበብምእመናንም አቤቱ ይቅር በለን እያሉ በመስገድ ይጸልያሉ፡፡

             ከዚያም ሁለተኛው ሥርዓተ ስግደት ይጀመራል፡፡ ዜማው የሚጀመረው አሁንምበቀኝ በግራ በመቀባበል ነው፡፡ አንዱ ይመራል ሌላው ይቀበላል፡፡ እንዲህ በማለት


ኪርያላይሶን /5 ጊዜበመሪ በኩል
ኪርያላይሶን/2 ጊዜዕብኖዲ ናይን በተመሪ በኩል
ኪርያላይሶን ታኦሰ ናይን
ኪርያላይሶን ማስያስ ናይን
ኪርያላይሶን ኢየሱስ ናይን
ኪርያላይሶን ክርስቶስ ናይን
ኪርያላይሶን አማኑኤል ናይን
ኪርያላይሶን ትስቡጣ ናይን

                 
በዚህ መልኩ አንድ ጊዜ ከተዘለቀ በኋላ እንደገና ይደገማል። በመጨራሻምበግራ በቀኝ በማስተዛዘል አርባ አንድ ጊዜ እየተዜመ ይሰገዳል። ከላይ የተጠቀሱት የጌታችንኅቡዓት ስሞች ናቸው። ኪራላይሶን ማለት አቤቱ ይቅር በለን ማለት ነው። በመቀጠልመልክአ ሕማማት በሊቃውንት ይዜማል ፤ከዚያም ካህኑ ፍትሐት ዘወልድ፣ ጸሎተ ቡራኬ፣ወዕቀቦሙ፣  ሥሉስ ቅዱስ፣  ማኅበራኒሁ ለክርስቶስ፣ ነዋ በግዑ የተሰኙ ምንባባትንእያፈራረቁ ያነባሉ። ካህኑም በጸሎታቸው ፍጻሜ 41 ኪራላይሶን በሉ ብለው መልእክትያስተላልፋሉ። ሕዝቡም መልእክቱን ተቀብሎ ይጸልያል። ዲይቆኑም “ሑሩ በሰላምእግዚአብሔር የሀሉ ምስሌክሙ፤ ንዑ ወተጋቡኡ ውስተ ቤተ ክርስቲያን በጊዜ ሠልስቱሰዓት ”ብሎ ያሰናብታል። 

             አሁን የተመለከትነው ሥርዓት ሰኞ በነገህ /በጠዋትየሚከናወነውን ነው። በሦስት፣በስድስት፣ በዘጠኝ፣ በአስራ አንድ ሰዓት የሚከናወነው ሥርዓትም አሁን በተመለከትነውመሠረት ነው። የሚለያዩት ምንባባቱ ብቻ ናቸው። የሰሙነ ሕማማት ዜማም ከሰኞ እስከረቡዕ ግእዝ፣ ሐሙስ አራራይ፣ ዓርብና ቅዳሜ እዝል ነው። አሁን በተመለከተነው መሠረትሰኞ  ማክሰኞ፣ ረቡዕ ከምንባባቸው በቀር ከላይ በተመለከትነው አኳኋን ሥርዓታቸውይፈጸማል። አሁን ደግሞ የምንመለከተው ሥርዓተ ጸሎተ ሐሙስን ነው።

ሥርዓተ ሰሙነ ሕማማት .....(ክፍል ሁለት)



 ጸሎተሐሙስ

 በብሉይ ኪዳን የቂጣ በዓልየሚለውን ትርጉምከመስጠቱ በተጨማሪጌታችን ምስጢረ ቁርባንንከምስጢረ ጸሎት ጋርአዋሕዶ የገለጠበት ዕለትስልሆነ ታላቅ የምስጢርቀን ነው። በዚህ ዕለትስግደቱ፣ ጸሎቱ፣ ምንባባቱእንደተለመደውይከናወናሉ ለየት ያለውሥርዓት መንበሩ /ታቦት/ጥቁር ልብስ ይለብሳል ጸሎተ ዕጣን ይጸለያል ቤተክርስቲያኑ በማዕጠንት ይታጠናል።

በዘጠኝ ሰዓት

              ዲያቆኑ ሁለት ኮስኮቶችን ውኃ ሞልቶ ያቀርባል አንዱ ለእግር፣ አንዱ ለእጅመታጠቢያ  ጸሎተ አኮቴት የተባለ የጸሎት ዐይነት ተጸልዮ ወንጌል ተነቦ ውኃው በካህኑ/በሊቀ ጳጳሱ/እጅ ተባርኮ የሕጽበተ እግር ሥርዓት ከካህናት እስከ ምእመናን  ከወንዶችእስከ ሴቶች በካህኑ እስተናጋጅነት ይከናወናል።

            ሥርዓተ ኅጽበቱ የሚከናወነውም ውኃ ብቻ ሳይሆን የወይራና የወይን ቅጠልንምለሥርዐቱ ማስፈጸሚያነት እንጠቀምባቸዋለን። ምስጢሩም የሚከተለውን ይመስላል። ወይራጸኑዕ ነው ክርስቶስ ጽኑ መከራ መቀበሉን ከማስረዳቱ በተጨማሪ እኛም /የሚያጥበውናየሚታጠበው ክርስቲያንመከራ ለመቀበል ዝግጁ ነን ለማለት ነው። የወይኑ ቅጠል በወይንየተመሰለ ደሙን አፍስሶ ለምእመናን የሕይወት መጠጥ ይሆናቸው ዘንድ መስጠቱን ለማዘከርነው። (ማቴ 2626.)

            ይህም ሥርዓት ጌታችን የደቀ መዛሙርትን እግር በማጠብ ያሳየውን የተግባርትምህርት ለምእመናን ለማሳየት ነው። ዮሐ 1314 በቀኝና በግራ የቆሙ ሊቃውንትም«ሐዋርያቲሁ ከበበ እግረ አርዳኢሁ ሐጸበ» እያሉ ይዘምራሉ። ይህ ሥርዓት ከተጠናቀቀበኋላ ሥርዓተ ቅዳሴው ተከናውኖ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ምእመናን ይቀበላሉ።

የጸሎተ ሐሙስ ቅዳሴ

            ቅዳሴው የሚከናወነው በተመጠነ ድምጽ ነው በቀስታ ስለሚጮህ ነው። የድምጽማጉያ አይጠቀሙም ምክንያቱም ዲያቆኑና ካህኑ ዜማውን በቀስታ የሚሉት ይሁዳበምስጢር ጌታችንን ማስያዙን ለመጠቆም ሲሆን በሌላ በኩል የዘመነ ብሉይ ጸሎት ዋጋውምድራዊ እንደነበር ለማስታወስ ነው።

            በመቀጠል ክቡር ይእቲ፥ ዕጣነ ሞገር ዝማሬ የተባሉ የድጓ ክፍሎች ተዘምረውአገልግሎቱ ይጠናቀቃል። ሕዝቡም ያለ ኑዛዜና ቡራኬ ይሰናበታሉ።

ዕለተ ዓርብ ነግህ

             ዕለተ ዓርብ የአዳምን ነጻነት ለመመለስ የአዳምን ዕዳ በደል አምላካችንየተሸከመበት ዕለት የኀዘን ዕለት የድኅነት ዕለትም ነው። በዚሁ ዕለት ሁሉም ነገርእንደተለመደው ይከናወናል መሪው እዝል ይመራል ሕዝቡ ይከተላል አራቱ ወንጌላትይነበባሉ። በየመሀሉ «ውጸቡሖ ተማከሩ ሊቃነ ካህናት፣ ሲነጋም ሊቃነ ካህናት ተማከሩ»የሚለው ዜማ በመሪ በተመሪ በሕዝብ ተሰጥዎ ይከናወናል። ምንባቡም ስግደቱም ድጓውምእንደ አለፈው ይቀጥላል።

በሦስት ሰዓት

              ሥዕለ ስቅለቱ መስቀሉ ወንጌሉ መብራቱ ጽንሐሑ በመቅደሱ በር ላይ ይዘጋጃልዲያቆኑ በቃለ ማኅዘኒ በሚያሳዝን ቃል ግፍኦሙ እግዚኦ ለእለ ይገፍኡኒ ይላል። ካህናቱምምእመናኑም በዜማ እየተቀበሉ ይሰግዳሉ።

ምስባክ ተሰብኮ አራቱ ወንጌላት ይነበባሉ። በየመሀሉ የሰዓቱ ድጓ ይቃኛል።

ስድስት ሰዓት

            የዕለቱ መሪ እዝል ይመራል ሦስቱ ካህናት ጽንሐሑን ይዘው ከርቤ እያጠኑዲያቆናት መብራት እያበሩ ለመስቀልከ ንስግድ እያሉ ያዜማሉ ምእመናን ዜማውንእየተቀበሉ ይሰግዳሉ ከዚያም ዲያቆኑ ቀነውኒ እደውየ ወእገርየ የሚለውን ምስባክ ሰብኮአራቱ ወንጌላት ይነበባሉ በየመሀሉ ድጓው ይዜማል ከዚህ ቀጥሎ ምእመናን ይቀመጣሉሦስቱ ካህናት ጥቁር ልብስ ለብሰው በሚያሳዝን ዜማ አምንስቲቲ ሙኪርያ አንቲፋሲልያሱ፣ ጌታየ ሆይ ስለ እኔ ሞትህ ወዮ እኔ ልሙትልህ እያሉ ሦስት ጊጌ ያዜማሉ።

           ሕዝቡ ይቀበላል በዚያው አያይዘው ተዘከረነ እግዚኦ በውስተ መንግስትከ እያሉበዜማ ይጸልያሉ ሕዝቡ ይቆማል ሥርዓተ ስግደቱም ይከናወናል።

በዘጠኝ ሰዓት

            ሌላው እንደተለመደው ሆኖ  ዘጥዕመ ሞተ በሥጋ ሦስት ጊዜ ካህናቱ በዜማይሉታል ምእመናንም ይቀበላሉ ምስባክ ተሰብኮ አራቱ ወንጌላት ይነበባሉ ስግደትእንደተለመደው ነው  በሦስት ሰዓት  በስድስት ሰዓት  በዘጠኝ ሰዓት  ወንጌላቱ ተነበውእንዳለቁ ለምእመናን ትምህርተ ወንጌል ይሰጣል። ይህ ግን እንደ ቋሚ ሥርዐት ሳይሆን እንደሁኔታው አመቺነት ነው።

አሥራ አንድ ሰዓት
             ካህናት በአራቱ መዓዘን ቁመው አራት መቶ እግዚኦታ ያደርሳሉ ዕለቱንየሚመለከቱ መዝሙራት ተመርጠው ይነበባሉ። ንሴብሖ እየተባለ ቤተ መቅዱስን በመዞርበከበሮ በጽና ጽል በሕማሙ ያዳነን እግዚአብሔር ይመሰገናል። ዑደት የሚደረገው ሥነስቅለቱን በመያዝ ነው። ምእመናን በሰሙነ ሕማማት የሠሩትን ኃጢያት እየተናዘዙ በክህናትአባቶች ንስሐ ይቀበላሉ፤ በወይራ ቅጠልም ቸብ ቸብ ይደረጋሉ የመከራው ተሳታፊዎችመሆናቸውን ለመግለጥ ነው። በታዘዙት መሠረትም ስግደታቸውን ያጠናቅቃሉ።

             ከዚያ በኋላ በካህኑ ኑዛዜ ምእመናን ወደ የቤታቸው ይሰናበታሉ። መስቀል መሳለምአሁንም የለም የቻለ ከሐሙስ ጀምሮ አሊያም ከዓርብ ማታ ጀምሮ እስከ ዕለተ ትንሣኤውድረስ ያከፍላል/ይጾማልየተጀመረውም በዕለተ ስቅለቱ በሐዋርያትና በእመቤታችንእንደሆነ አበው ያስተምራሉ።

ቀዳም ሥዑር

             የማትጾመዋ ቅዳሜ ስለምትጾም “ስዑር /የተሻረች/” ተብላለች በዓል መሻርንአይመለከትም። ቀዳም ሥዑር በጾም ምክንያት የተሻረችው ቀዳሚት ሰንበት ሌሊት ሥርዓቱየሚጀመረው በመኅልየ ሰሎሞን ምንባብ ነው። ማኅሌቱም እዝሉ እየተቃኘ፣ እየተመለጠነ፣እየተዘመመ እየተመረገደ እየተጸፉ ያድራል ጥዋት አቡን መዋሥዕት ውዳሴ ማርያም ዜማተደርሶ ወለመልአከ ሕይወትስ ሰቀልዎ በሚለው ሰላም ይጠናቀቃል። ገብረ ሰላም በመስቀሉእየተባለ እየተዘመረ ቀጤማውም ቤተ መቅደሱን ዞሮ በካህኑ ተባርኮ ለምእመናን ይታደላል።የቀጤማው አመጣጥና ምስጢርም ከአባታችን ከኖኅ ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው ምድር በማየአይኅ /በጥፋት ውኃበጠፋችበት ወቅት የኖኅ ታማኝ መልእክተኛ ርግብ የውኃውን መጉደልያበሰረችው ቀጤማ ይዘ በመግባት ነው።

              ዛሬም ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች የኃጢአት ውኃ ጎደለ፣ የኃጢአት ውኃ ጠፋበክርቶስ ሞትና ትንሣኤ ነጻነት ተሰብከ ታወጀ በማለት ካህናት ቀጤማ ይዘው ምእመናንንያበሥሩታል። በአጠቅላይ ሥርዓተ ሕማሙን፣ ሰሙነ ሕማማት ብለው የተለየ ሥርዓትአውጥተው አባቶቻችን ተግተው ያቆዩልንን ሥርዓተ መላእክት ልንጠብቀውምልንጠቀምበት ይገባል።

ለብርሃነ ትንሳኤው በሰላም ያድርሰን
መልካም ሰሙነ ሕማማት!!!

No comments:

Post a Comment