Friday 23 December 2011

የምእመናን መሰባሰብ፤ የቅዳሴ ቀዳሚ ምስጢር


የምእመናን መሰባሰብ፤ የቅዳሴ ቀዳሚ ምስጢር

ታኅሣሥ 13/2004 ዓ.ም
በዲ/ን በረከት አዝመራው

ቅዳሴ የአንዲቷ ሰማያዊት ቤተ ክርስቲያን እውነተኛ ገጽ እንደሆነ ሁሉ የምእመናን መሰባሰብ ደግሞ የቅዳሴ የመጀመሪያ መሠረት ነው፡፡ kidaseበመሰባሰብ የፈጸመው የቅዳሴ ሥርዓታችን አስቀድሞም በቅዱሳን መላእክት ዓለም የነበረና በምድር ባለች መቅደሱም በምእመናን መሰባሰብ የሚፈጸም ነው፡፡ “እኔ በመካከላቸው እሆናለሁ” ብሎ ደስ የሚያሰኝ ዘላለማዊ ቃል ኪዳን የገባልን ጌታችን፣ “ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰበሰቡበት” በማለት መሰባሰባችን ጸጋና ረድኤቱን እንድናገኝ ምክንያት መሆኑን ነግሮናል /ማቴ.18፥20/ በዚህ ርዕስም የጌታን ቃል በታላቅ ትጋት በፈጸመች ሰማያዊ ሥርዓቷን ከቅዱሳን መላእክት ዓለም ያገኘች፣ የምስጋና ሥርዓቷም በትውፊት ደርሶ ለቤተ ክርስቲየን መሠረት በሆነው በጠንታዊት /በሐዋርያት ዘመን/ ቤተ ክርስቲያን ለምእመናን መሰባሰብ ይሰጥ የነበረውን ትኩረትና ምስጢራዊ እይታ እንመለከታለን፡፡



የምእመናን መሰባሰብ በቅዳሴ ጥንታዊ ትውፊት

ተሰባስቦ እግዚአብሔርን ማመስገን መሥዋዕትን ማቅረብ አስቀድሞ በብሉይ ኪዳንም በምሳለ የቆየ ቢሆንም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሐዋርያት ጋር በቤተ አልዓዛር የአይሁድን ፋሲካ ሲያከብር የአማናዊው ቅዳሴ መሠረት ተጣለ /ሉቃ.22፥7/፡፡ የቤተ እስራኤል ጉባኤ መሠረት ይሆኑ ዘንድ ዐሠራ ሁለቱን የያዕቆብ ልጆች የመረጠ እግዚአብሔር እስራኤል ዘነፍስ የተባሉ የምእመናን ጉባኤ የሆነች የቤተ ክርስቲያን መሠረቶች የሆኑ ሐዋርያትን ሰብስቦ በመንግሥተ ሰማያት ማዕድ ላይ አስቀመጣቸው /ሉቃ.22፥29-30/፡፡ በዚህም በሐዋርያት በኩል የቤተ ክርስቲያን አንድነት መመሠረቱን እንመለከታለን፡፡ በመንፈስ ቅዱስ መምጣት /ጸጋውን ረድኤቱን በመቀበል/ የጌታን ምስጢር ሁሉ የተረዱት ሐዋርያት አባቶቻችንም የቅዳሴን ምስጢር ምእመናንን ሰብስበው በአንድነት የሚፈጽሙ ሆነዋል /የሐዋ.20፥2/፡፡
ይህ ሥርዓት በሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን በእርግጥም የጸና ሆኗል፡፡ “ለእናንተ ደግሞ አሳልፌ የሰጠሁትን እኔ ከጌታ ተቀብያለሁና” የሚለው ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ “በመጀመሪያ ወደ ማኅበር ስትሰበሰቡ…” በማለት በእርሱ ዘመን የምእመናን መሰብሰብ ለዐበይት ሃይማኖታዊ ሥርዓቶች ቅድመ ሁኔታ እንደነበረ ይናገራል /1ቆሮ.11-18/፡፡ “ለእናንተ ደግሞ አሳልፌ የሰጠሁትን እኔ ከጌታ ተቀብያለሁና” በማለቱም ይህ በሥርዓተ ቅዳሴ በቤተ ክርስቲያን የመሰባሰብ ምስጢር ከዚያ በኋላ ሥርዓቱን ጠብቆ በትውፊት የሚተላለፍ ሆኗል፡፡
የሐዋርያት ተከታዮች የሆኑ አበውም ይህን የሐዋርያት ትውፊት ተቀብለው በቀጥታ ለትውለድ አስተላልፈዋል፡፡ ይህንንም “ትምህርታችን ከቅዳሴ ጋር የተስማማ ቅዳሴያችንም ትምህርታችንን የሚያጸና ነው” ብለው አጽንተውታል፡፡ /St. Iranaeus, Against Heresies 4:18-5/ /ማቴ.18፥ 20/፡፡


በዚህ ዘመን ምእመናን ሁሉ በቅዳሴ ተገኝተው ሁሉም ሥጋወደሙ ተቀብለው ይሔዱ ነበር፡፡ የታመመ እንኳ ቢኖር ሔደው ያቀብሉት ነበር፡፡ ያለሕማምና ከባድ ችግር ቅዳሴ የቀረ ሰው ራሱን አውግዞ ከቤተ ክርስቲያን እንደለየ ይቆጠር ነበር /fr.Alexander Schmemann, Eucharist, pp.24/፡፡

ሥርዓተ ቅዳሴ የሁሉም ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያን ሕንፃም ይህን ለማስፈጸም አመቺ ተደርጐ ይሠራ ነበር፡፡ ይህ ጥንታዊ የሕንፃ ቤተ ክርስትያን አሠራር ትውፊት አሁንም በቤተ ክርስቲያናችን በግልጽ ያለ ነው፡፡ ቅዳሴ ወንዶች፤ ሴቶች፣ ሕፃናት ሁሉ ሊሳተፉት የሚገባ ምስጢር ባይሆን በቤተ ክርስቲያን ካህናት፣ ወንዶች፣ ሴቶች የሚቆሙበት ቦታ ለይቶ ማዘጋጀት ለምን ያስፈልግ ነበር? ይህ የሆነው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ፣ የክርስቶስ አካል የሆነች የምእመናን አንድነት ማሳያ ስለሆነ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ አካል ናት ስንል ሁሉንም ምእመናን አቅፋ የያዘች መሆኗን እንደሚገልጽ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን የዚህ መገለጫ ከሆነ ሁሉን ሊይዝ ይገባዋልና፡፡

በቅዳሴ ጊዜ ስላለው የምእመናን ኅብረት /ስብስብ/ የጥንታዊት ቤተ ክርስቲያን እይታ ከዚህም የመጠቀ ነበር፡፡ በጥንታዊት ቤተ ክርስቲያን የምእመናን ስብስብ ምድራውያንን ብቻ ሳይሆን ሰማያውያንንም ያጠቃለለ እንደሆነ ይታመን እንደነበር በምርምር በተገኙ ጥንታውያን ሥዕሎች ይታያል፡፡ በልባዊ እምነታቸው በጥልቀት ያለውን የእነርሱን እና የሰማያውያንን ኅብረት በሥዕል ያሳዩ ነበር፡፡ አንድ የነገረ ቤተ ክርስቲያን ሊቅ ይህን ሲገልጹ “በብዙ ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት ሥዕላቱ ከማኅበረ ቤተ ክርስቲያን ጋር የሚሳተፉ፣ የዚህን ምስጢር ትርጉም የሚናገሩ፣ ዘላለማዊ እንቅስቃሴውንና መስመሩን የሚያሟሉ እንደሆነ እንረዳለን” ይላሉ /Alexander schememann. The Euchrist pp.21/
ይህ ሥርዓት አሁንም በቤተ ክርስቲያናችን ይታያል፤ ይጠበቃልም፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን ጥንታዊ ትውፊት መሠረትም ቅዱሳት ሥዕላት ቅድስትና መቅደሱን በሚለየው ግድግዳ ላይ ይሣላሉ፡፡

ከዚህም በተጨማሪ ሌላ ምስክር አለን፡፡ ሥርዓተ ቅዳሴአችን ይዘቱና አፈጻጸሙ እንደሚያመለክተን እያንዳንዱ የካህን ጸሎት እየንዳንዱ የዲያቆን ትእዛዝ በምእመናን መልስ /አሜን/ ይጸናል፤ ይፈጸማል፡፡ በመጽሐፈ ቅዳሴ የምናነበው “ይበል ካህን፣ ይበል ሕዝብ…” የሚሉት ትእዛዛትም ለዚህ ምስክር ናቸው፡፡ በዚህም ሥርዓተ ቅዳሴ የካህናት ብቻ ሳይሆን የምእመናንና የካህናት የአንድነት ምስጢር መሆኑን እንረደለን፡፡

ይህንን የአንድነት ምስጢር ለማጽናት በፍትሐ ነገሥቱ ስለቅዳሴ በተነገረበት ክፍል “ምእመናን ሳይሰበሰቡ ቅዳሴ የሚጀምር አይኑር” የሚለው መልእክት እዚህ ላይ ልብ ይሏል፡፡

በዘመናችን የሚታየው የቅዳሴን ለካህናትና ለተወሰኑ ሰዎች መተው፣ ለቤተ ክርስቲያን ሥርዓትና የሕይወት ልምድ እንግዳ የሆነ ስርዋጽ ነው፡፡ አንዳንዶች ሥርዓተ ቅዳሴ በዋነኝነት የካህናት ሥራ እንደሆነ እና እነርሱ ግን ቢኖሩም እንኳን አዳማጭ፣ አዳማቂ እንደሆኑ ያምናሉ፡፡ ይህ አስተሳሰብ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ከውስጧ ከሚሰሟት ሕመሞች አንዱ ነው፡፡ አንዳንዴ ለሚታየው በሥርዓተ ቅዳሴ በንቃት አለመከታተል፣ ከዚህም የተነሣ የመንፈሳዊ ሕይወት መድከም፣ አንዱ ምክንያት መሆኑን መረዳት ይገባል፡፡

የመሰባሰባችን ምስጢር

የምእመናን አንድነት፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ አካል ናት፡፡ እያንዳንዱ ምእመን ደግሞ የክርስቶስ ብልት ነው /1ቆሮ.12፥27/፡፡ እንግዲህ በምእመናን መሰባሰብ፣ ከምድራዊ አስተዳደራዊ ተቋም በተለየ የላቀች ቅድስት የሆነች የክርስቶስ አካል፣ የቤተ ክርስቲያን የአንድነቷ የቅድስናዋ ታላቅ መዓርግ /ፍጻሜ/ ይሆናል፡፡

“የቤተ ክርስቲያን ፍፁምነት” ማለትም ቅድስት የሆነች የቤተ ክርስቲያን በሰማያዊ ገጽታዋ መገለጥ ማለት ነው፡፡ የምእመናን ስብሰብ እንደማንኛውም ምድራዊ ስብስብ የሺህዎች “ድምር” ማለት ሳይሆን የክርስቶስ ሰማያዊ አካል /በስሙ በማመን ብልቶቹ የሆኑ ምእመናን ኅብረት/ መገለጥ ነውና፡፡

ብዙ የቤተ ክርስቲያንን ጥንታዊ ትውፊቶች የማይቀበሉ አዳዲስ የሥነ መለኮት አስተምህሮዎች ብቅ ብቅ ባሉበት በዘመናችን ይህን ጠንቅቀን ማወቅ ይገባናል፡፡ እነዚህ ምድራውያን አስተምህሮዎች ለአምልኮ ሥርዓት ግድ የሌላቸው፣ ቢኖራቸው እንኳ አንዱን የቅዳሴ ክፍል ከሌላው የሚያበላልጡ፣ አንዱን በጣም አስፈላጊ አንዱን ደግሞ ብዙም የማያስፈልግ አያደረጉ መመደብ የሚቀናቸው ናቸው፡፡ ስለቅዳሴ ብንጠይቃቸው ሕብስቱና ወይኑ የሚለወጥበትን ጊዜ አጉልተው ሌላውን አሳንሰው የሚናገሩ ናቸው፡፡ ሕብስቱና ወይኑ የመለወጡን ነገርም ቢሆን በኦርቶደክሳዊና ሰማያዊ መንገድ ሳይሆን በሳይንሳዊና ምድራዊ መንገድ ለማረጋገጥና ለመተንተን የሚፈልጉ ናቸው፡፡ እነዚህ አስተምህሮዎች በቅዱሳት መጻሕፍት ተቀባይነት የሌላቸው ናቸው፡፡

ይህን ሰማያዊ ምስጢር የምታውቅ ጥንታዊት ቤተ ክርስቲያን የአንድ ምእመን ከቅዳሴ መቅረት በጣም ያስጨንቃት ነበር፡፡ ከማኅበሯ የማያስገድድ ምክንያት የሚቀሩ ሰዎችን በቆራጥ እርምጃ ታሰናብት ነበር፡፡ /fr. Alexander Schememan, the Eucharist, pp21/ ይህ ጥንታዊ መረዳት፣ ይህ ጥንታዊ መንፈሳዊ ተግባር በዘመናችን የተረሳ ይመስላል፡፡ የዚህን ዝለት፣ የዚህን ቸልተኝነት ውጤትም ማንም ሊነግረን አይገባም፤ እያንዳንዳችን በራሳችን የመንፈሳዊ ሕይወት ቀውስ እናውቀዋለንና፤

ለቅዳሴ ስንሰባሰብ ከዚህ ዓለም ያልሆነች፣ ነገር ግን ስለ ዓለም መዳን በዚህ ዓለም ውስጥ ያለች ሰማያዊቷ የክርስቶስ አካል ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን “እየገነባን /እየሆንን/” መሆኑን ልናውቅ ይገባል፡፡ ይህን አስመልክቶ አንድ ኦርቶዶክሳዊ ሊቅ “ወደ ቤተ ክርስቲያን እየሔድኩ ነው ስል ከእነርሱ ጋር ሆኜ ቤተ ክርስቲያንን ለመገንባት፣ በጥምቀት ብልት የሆንኩበትን፣ በቃሉ ምሉዕና ፍጹም ትክክለኛ ትርጉም፣ የክርስቶስን አካል፣ ለመሆን ወደ ምእመናን ጉባኤ እየሔድኩ ነው ለማለት ነው፡፡” ይላሉ፡፡ /fr. Alexander Schememan, The Eucharist, pp21/

የቤተ ክርስቲያን ቅድስና ይህ ነው፤ የክርስቶስ አካል መሆኗ፡፡ እያንዳንዳችን ምንም ያህል ኀጢአተኞች ልንሆን እንችላለን፤ ነንም፡፡ የምእመናን አንድነት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ግነ ንጽሕት ቅድስት ናት፡፡ ይህም ከእኛ የመጣ ቅድስና ሳይሆን አካሉ በሆነች በቤተ ክርስቲየን “ራሷ” ሆኖ በመካከላችን ካለው ክርስቶስ የተገኘ ነው፡፡ ከኀጢአት የማንጠራ /የማንርቅ/ ጎስቋሎች ብንሆንም በመሰባሰባችን “የምትመሠረት” ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ግን በእውነት ንጽሕት ናት፤ የሕመሟ መድኀኒት፣ የቅድስናዋ ምንጭ በመካከሏ ነውና፡፡ በምእመናን መሰባሰብ “የተገነባች” ቤተ ክርስቲያን “ቅዱስ ሕዝብ፣ የንጉሥ ካህናት፣ የተመረጠ ዘር….” መባል ይገባታል፤ የመረጣት ከኀጢአት ባርነት አውጥቶ ያከበራት የቅድስናዋ አክሊል በመካለሏ ነውና /1ጴጥ.2፥9/፡፡ ለዚህ ነው በሐዋርያት ዘመን የነበሩ ምእመናን “ቅዱሳን” ይባሉ የነበሩት፤ በመሰባሰብ ይኖሩ ነበረና /ፊልሞ.1፥7/፡፡

ይህ መሰባሰብ የቅድስና መዓዛ ነው፡፡ ይህ ሰማያዊ ደስታ ነበረ መራራውን መከራ በደስታ እንዲቀበሉት ያስቻላቸው፡፡ ይህ የቅድስና ጉባኤ የቤተ ክርስቲያን ሰማያዊ ደስታ ነበር፡፡ በአስቸጋሪው ዓለም ክርስትናን በቆራጥነት እንዲሰብኩ ያስቻላቸው ታላቅ አንድነት ከዚህ የመነጨው ፍቅረ ቢጽና ፍቅረ እግዚአብሔር ነው፡፡ “ፍፃሜ ማኅበርሃ ለቤተ ክርስቲያን፣ የቤተ ክርስቲያን የማኅበሯ ፍጻሜ” ይህ ነውና፡፡

የምእመናን መሰባሰብ የክርስቶስን አካል እንደሚገልጥ፣ ቅዳሴውን የሚመራው ካህን ራስ የተባለ የክርስቶስን ክህነት ይገልጣል፡፡ /ኤፌ.5፥23፣1ቆሮ.11፥3/ በጸጋ በተሰጠው ሥልጣነ ክህነት ውስጥ ሆኖ /እያገለገለ// የክርስቶስን የባህርይ /ዘላለማዊ/ ክህነት ይመሰክራል፡፡ ካህኑ የሚለብሰው የክህነት ልብስ፣ ክርስቶስ በውስጧ ያደረው የቤተ ክርስቲያን መገለጫ ነው፡፡ ለዚህ ነው በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ምእመናን ሳይሰበሰቡ ልብሰ ተክህኖ መልበስ የተከለከለው፡፡ /መጽሐፈ ቅዳሴ/ በካህኑ ራስ ላይ ያለው አክሊል እንደ መልከ ጸዴቅ ሥርዓት ያለውን ዘለዓለማዊውን የክርስቶስ ክህነት ይመሰክራል፡፡ /ዕብ.7፥20-22፣ መዝ.109፥4፣ ዕብ.7፥1/ እንግዲህ የጌታችን ዘለዓለማዊ ክህነት በዘለዓለማዊና ሰማያዊ መቅደሱ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን /በምእመናን መካከል/ በዚህ መልኩ ይገለጣል፤ ቅዱስ ጳዉሎስ “እርሱ ግን የማይለወጥ ክህነት አለው” እንዳለ /ዕብ.7፥25/፡፡ ስለዚህ መሰባሰባችን ክርስቶስን በመካከላችን አድርገን ነው፡፡ ስለዚህ በቅዳሴ መሰባሰባችን በመካከላችን ካለው ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተነሣ በእውነት ታላቅ ነው፡፡

በመጨረሻ፣ እግዚአብሔር በማያሳየው ምድር በደስታ ይኖር ዘንድ አብርሃም ወገኖቹንና የአባቱን ቤት እንዲተው ከታዘዘ ወደ እግዚአብሔር መገለጫ፣ ወደ ጽዮን ተራራ ስንወጣ፤ የበኩራትን ማኅበር ልንመሠርት ስንሰባሰብ እንዴት ዓለማዊ ጣጣችንን አንተው? እስራኤል በሲና ተራራ በሚያስፈራ ሁኔታ የተገለጠውን እግዚአብሔርን ለመስማት ሦስት ቀን ከተዘጋጁ፤ ልብሳቸውን ካጠቡ፤ በሚያስደንቅ የመሥዋዕትነት ፍቅሩ ስለኛ የተሰቀለውን አምላካችንን ለማየት ብቻ ሳይሆን ለመብላት ለመጠጣት ስንሰባሰብ ምን ያህል መዘጋጀት፣ ልብሳችን ብቻ ሳይሆን ሥጋውንና ደሙን ሰውነታችንን ምን ያህል በንስሐ ማጠብ ይገባን ይሆን? /ዘፍ.12፥1፣ ዕብ.12፥22-24፣ ዘፀ.19፥14-15/ ሕፃኑ ሳሙኤል በቤተ መቅደስ ለሚጠራው ቃል በንቃት መልስ ከሰጠ፤ በእውነተኛ ቤተ መቅደሱ የተሰበሰብን እኛ በቅዳሴ ሰዓት በልዩ ልዩ መንገድ ለሚሰማው የእግዚአብሔር ድምፅ ምን ያህል በትጋትና በንቃት መልስ መስጠት ይኖርብን ይሆን? /1ኛ. ሰሙ.3፥1-14/ በእውነት እግዚአብሔር ከዚህ ሰማያዊ ጉባኤ አይለየን፡፡ ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

No comments:

Post a Comment